ቤተሰብ የሚለው ቃል በፍቺ እና በምሥጢር ሲተነተን ወደላይም ፣ ወደታችም ፣ ወደፊትም ወደኋላም ወደግራም ወደቀኝም ያለውን ሥጋዊ እና የመንፈሳዊ የተዛምዶ ምልአተ ጉባኤ ያሟላና ያካተተ ስም ነው፡፡
ከላይ ወደታች ያለው የቤተሰባዊ ስም ሲብራራ የአቶ እገሌ ፣ የወ/ሮ እገሊት ልጆች ፣ ወደ ግራ እና ወደቀኝ ያለው ቤተሰባዊ ስያሜ ሲገለጽ እነ እገሌ ፣ እነ እገሌ የእነ እገሌ እህት ፣ ወንድም ፣ አክስት ፣ አጎት ፣ የእህት ልጅ ፣ የወንድም ልጅ ፣ ወ.ዘ.ተ በማለት በሁሉም አቅጣጫ ያለውን የሥጋዊ የቤተሰብ የተዛመደ ሐረግ መግለጽ ይቻላል፡፡ ከሥጋዊ ቤተሰብ ትሥሥር ይልቅ መንፈሳዊ ቤተሰብነት የእግዚአብሔር ቤተሰቦች ፣ የድንግል ማርያም ቤተሰቦች ወ.ዘ.ተ በማለት ሰፍቶና ጎልቶ ይገለጻል፡፡
በዚህ መሠረት የቅዱስ ያሬድ ቤተሰብ ማለት ወደ ላይ የፈጠረው ፣ የመረጠው ሰማያዊ ምስጢርን የገለጠለት እግዚአብሔር ፤ ወደጎን እንደነሱ በእነርሱ ምስጋና እግዚአብሔርን እንዲያመሰግን ያስተማሩት እና የረዱት ቅዱሳን መላእክት ፣ ወደታች የእርሱን ሰማያዊ ምስጋና የዜማ ምሥጢር ቁጥሩን ሳያጎድሉ ፣ ብዛቱን ሳይቀንሱ ሥርዓቱን ሳይቀይሩ ፣ ሕጉን ሳያፈርሱ ፣ ሰማያዊነቱን መንፈሰዊነቱን ሳይሽሩ ፣ በሙሉተምረው አውቀው በሙሉ የሚያስተምሩ እና በሙሉ እግዚአብሔርን የሚያሰግኑ እንዲሁም በቅዱስ ያሬድ ምስጋና ሰማያዊ ድርሰት የእግዚአብሔርን አምላክነት የሚያምኑና የሚመሰክሩ ፣ የቅዱስ ያሬድ ዜማው እንዲስፋፋ፣ታሪኩ እንዲታወቅ ፣ በእውቀታቸው ፣ በጉልበታቸው ፣ በገንዘባቸው እና በጸሎታቸው የሚያገለግሉ የቅዱስ ያሬድ ቤተሰብ ይባላሉ፡፡